GROW WISER AT THE WATER TOWER
Staff Academic Administrative Graduate
ቋንቋና ስነ ጽሑፍ ትምህርት ክፍልን ለማስተዋወቅ “የግእዝ ቋንቋና ሀገራዊ ፋይዳው” በሚል መሪ ሀሳብ ከክልል ትምህርት ቢሮ ፣ ከዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ እና የሃይማኖት አባቶች እንዲሁም ተማሪዎች በተገኙበት የውይይት ዓውደ ጥናት ተካሄደ ፡፡
በዚህ ዐውደ ጥናት ላይ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው አካ/ጉ/ም/ ፕሬዚዳንት ይኽይስ አረጉ (ዶ/ር) እንደገለጹት ዛሬ የተገናኘነው ለዘመናት ተረስቶ ስለቆየው ሀገር በቀል ቋንቋ ለመወያየትና ለማስተዋወቅ ብሎም ወደ ቀደመ ክብርና ከፍታችን ወደ ማንነታችን ለመመለስ፣ የአባቶቻችንን እሴቶች ለመገንባትና ለመጠበቅ ለተተኪ ትውልድ ለማስተላለፍ ነው፡፡ ከዕውቀት፣ ከፍልስፍናና ከጥበብ ርስታችንም ጭምር ተነቅለን ቆይተናል፤ እኛም ትውልዱም ተጎድቶ ቆይቷል፤ ነገር ግን ከዚህ በኋላ ማህበረሰቡንና ሕጻናትን መታደግ ከቻልን ከዚህ ሀገር በቀል ቋንቋ የምናተርፈው ዕውቀት ብዙ ነው ፡፡
የራሳችንን ቋንቋ ትተን በሌሎች ዓለማት ቋንቋዎች ስንማር፣ስንመራመር ቆይተናል፤ ነገር ግን ዛሬ በራሳችን ቋንቋ መማርና መመራመር መጀመራችን ወደ ቀደመ ከፍታችንና ታሪካችን ለመመለስ አንዱ ማሳያ ነውና ይህ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል፡፡
የግእዝ ቋንቋ ኪነ-ህንጻውን ስነ-ጽሁፍፉን፣ ስነ-መለኮቱን፣ ስነ-ቅመማውን ሲሰራ ከቆየ በኃላ በታሪክ አጋጣሚ ከቤተ መንግስት ወጦ በቤተ ክርስትያን ብቻ መቀመጥ ቻለ፤ በዚም ሁኔታ ስልጣኔያችን ተዳከመ። ሙሉ የሆነው ቋንቋ ጠፋ ኢትዮጵያ ራሷ ጠፍቷት ራሷን ለመፈለግ ዓለምን የምትዞር ሀገር ናት ። በመሆኑም አሁን ላይ የራሷን ቋንቋ በመፈለግ ላይ ትገኛለች በማለት ለተጋባዥ እንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁና የውይይቱን መክፈቻ ንግግር አድርገዋል፡፡
በዚህ የዐውደ ጥናት ላይ የግእዝ ቋንቋና ስነ ፅሑፍ ትምህርት ክፍልን አጀማመርና አጠቃላይ የግዕዝን ምንነት በተመለከተ መወያያ ፅሑፍ ያቀረቡት በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት ክፍል ተጠሪና መምህር መርጌታ አንሙት ዘመናይ እንዳሉት የግእዝ ቋንቋ ከ3 ሺ ዓመት በፊት ተግባራዊ የሆነ ቋንቋ ነበር። ብዙ ጊዜ መውደቅ መነሳት ያሳየ ቢሆንም ከአክሱም ዘመነ መንግስት ጀምሮ አሁን እስካለበት ጊዜ ድረስ 4 የውድቀት ደረጃዎችን ያሳየ ቋንቋ እንደሆነም አብራርተዋል፡፡ በአክሱም ዘመነ መንግስት ልሳነ ንጉስ ተብሎ ሀገራዊ ቋንቋ ሆኖ ሃይማኖታዊ እሴቶችን፣ ፖለቲካዊ፣ አሴቶች፣ ማህበራዊ የዳኝነት ስረዓቶች ሁሉም ተግባራት የሚካሄድበት ቋንቋ እንደነበር አውስተዋል ። የግእዝ ቋንቋ ስለ ህክምና ፣ስለ ዳኝነት ስርዓት፣ስለ ዘመን አቆጣጠር፣ ስለ ስነ-ፈለክ ስነ- ምርምር ስለ ስነ-ሰብ ወ.ዘ.ተ ዘመን ተሸጋሪ ስራዎች የተሰሩበት፣ ለኢትዮጵያ ብቻም ሳይሆን ለአለምም ጭምር የስልጣኔ በር የከፈተ፣ትውልድን በስነ-ምግባር የሚቀርፁና ሃገር ተረካቢ ትውልድ የሚያፈራ ታላቅ ቋንቋ እንደሆነ ገልፀዋል።
ከሌሎች ቋንቋዎች አንፃር ግእዝ ቋንቋ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው የልዩ ባህሪይ ባለቤትም ነው፡፡ የግእዝ ቋንቋ ለመረሳቱ በርካታ ምክንያቶች ቢኖሩም እንደ መነሻ የሚጠቀሱት የዮዲት ጉዲት ወደ ስልጣን መምጣት፣ እንዲሁም ነገስታት ከሌሎች ክፍለ ዓለማት ካሉ መንግስታት ጋር ያደርጉት የነበረው የደብዳቤ ልውውጥ ግእዝን በመተው በአማረኛ ቋንቋ በመጠቀም እና የአማርኛ ቋንቋ መስፋፋት በሌላ በኩል እንደ ላቶፕና መሰል ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶች መስፋፋት እና ግእዝ በቤተ ክርስቲያን ብቻ ተወስኖ መቀመጡ ተጠቃሽ ነጥቦች መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡
በባህዳር ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ የሆኑት ዶ/ር ሙሉቀን አንዷለም እና ዶ/ር አባ በአማን ግሩም #አባይን_በቅኔ እና #የፍልሰት_ምልሰት የተሰኙ ጥናታዊ ጽሑፎች በቅደም ተከተል ለውይይት ቀርበዋል።
በዚህ ዓውደ ጥናት ላይ በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ከደብረ ማርቆስ ከተማ ከአቡነ ጎርጎሪዎስ ት/ቤት በመጡ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤት ተማሪዎች እና ከተጋባዥ የቋንቋው ሊቃውንት ለታዳሚዎች ቅኔ የቀረበ ሲሆን በቀረቡ የጥናት ፅሑፎችና የመወያያ ነጥቦች ላይ ታዳሚዎች ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ሰጥተዋል፤ ምላሽና ማብራሪያም ከጥናት አቅራቢዎቹ ተሰጦባቸዋል፡፡
በዐውደ ጥናቱ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ የስረዓተ ትምህርት ዳይሬክቶሬት ሃላፊ አቶ ካሴ አባተ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው የግእዝ ቋንቋን ለማሳደግ እያደረገ ያለውን ተግባር አድንቀው በአማራ ክልልም አዲሱ ስረዓተ ትምህርት ተቀርፆ የግእዝ ቋንቋን እንደ አንድ የትምህርት አካል አደርጎ ለመስጠት በአማራ ክልል በተመረጡ 4 ዞኖችና 6 ትምህርት ቤቶች ማለትም በደቡብ ጎንደር፣ በባህር ዳር፣ በምስራቅ ጎጃም ደብረ ኤሊያስ ወረዳ በአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች በሙከራ ደረጃ በመሰጠት ላይ እንደሚገኝ ገልፀዋል፡፡ ይህን ተግባር በማጠናከር ከሌሎች ዩኒቨርሲዎች ጋር በመሆን በተመረጡ ት/ቤቶች የሚማሩ ተማሪዎችንና መምህራንን ማገዝና መርዳት ስረዓተ ትምህርቱ እንዲሻሻል ብርቱ ጥረት ማድረግ ለሀገሪቱም በሙያው የተማረ የሰው ሃይል ማፈራት ከዩኒቨርሲቲው እንደሚጠበቅበት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
መርሃ ግብሩ በንግግር የዘጉት የዩኒቨርሲቲያችን አካ/ጉ/ም/ፕሬዚዳንት ዶ.ር ይኽይስ አረጉ እንደገጹት ለታሪካችን፣ ለቅርሳችን፣ ለማንነታችን ታላቅ ስለሆነው ግእዝ ቋንቋ በዚህ መልኩ ልዩ ትኩረት ተሰጦት መወያየት መጀመራችን በራሱ ለዚህች ሀገር ግእዝ ትንሳኤ ይሆናል ብለው እንደሚምኑ እና በዩኒቨርሲቲያችንም ቋንቋን ማበልፀግ እንደ አንድ የልህቀት ማዕከል አድርጎ እየሰራበት እንደሚገኝ ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥልና የግእዝ ቋንቋ ትምህርት ክፍልም በሌሎች ዓለማት ለሚኖሩ ዜጎች ሁሉ በድጅታል ቴክኖሎጂ ትምህርቱን ለመስጠት በዝግጅት ላይ መሆናቸውንም አድንቀው በመጨረሻም በዚህ ዐውደ ጥናት ላይ ተገኝታችሁ ለተሳተፋችሁ አካላት ሁሉ ምስጋና ይድረሳችሁ በማለት ሀሳባቸውን አጠቃለዋል፡፡
ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የግእዝ ቋንቋን ለማሳደግና ተተኪ ምሁራንን ለማፍራት በ2014 ዓ.ም ትምህርት ክፍሉን በመክፈት ተማሪዎችን ተቀብሎ በመጀምሪያ ድግሪ በማስተማር ላይ ይገኛል፡፡
There are no upcoming events.
DMU Radio Broadcasting . . .