GROW WISER AT THE WATER TOWER
Staff Academic Administrative Graduate
ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ሐምሌ 19/2014 ዓ.ም (ደ.ማ.ዩ ህዝብ ግንኙነትና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት) ደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ በምስራቅ ጎጃም ዞን በተለይም ደግሞ በሸበል በረንታ ወረዳ እየተፈፀመ የሚገኘውን ጎጅ ልማዳዊ የደም መመላለስ ባህል ለማስቀረትና ማህበረሰቡ ሰላማዊ ህይወት እንዲኖረው ለማስቻል በዩኒቨርሲቲው ሐዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም በኩል የሁለት ዓመታት ፕሮጀክት በመቅረፅ በስፋት እየሰራ ይገኛል፡፡
በዚህም በ2013 እና በ2014 ዓ.ም የማህበረሰቡን አመለካከት በመለወጥ 59 እርቆች የተፈፅመው እና ቀያቸውን እርቀው የተበተኑ የገዳይና ሟች ቤተሰቦችም ወደ ቀያቸዉ ተመልሰዉ መደበኛ ኑሯቸውን እየመሩና ወደ ልማት እየተመለሱ እንደሚገኙ በአካል ተገኝተን ለማረጋገጥ ችለናል፡፡
ይህን የእርቀ ሰላም ሂደት በማስመልከት የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት ዶ/ር ታፈረ መላኩ፣ ም/ፕሬዚደንቶች፣ ዳይሬክተሮች፣ዲኖችና የልዩ ልዩ ስራ ክፍል ኃላፊዎችና ባለሙያዎች እንዲሁም የአማራ ክልል ፍትህ ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አያሌው አባተን ጨምሮ የምስራቅ ጎጃም ዞን ም/አስተዳዳሪ፣ የሸበል በረንታ ዋና አስተዳዳሪ እና የፀጥታ አካላት እንዲሁም የዚህ እርቅ ስነ ስርዓት ቀጥተኛ ባለጉዳዮች(ባለ-ደሞች) እና አስታራቂ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች እና ልዩ ልዩ የማህበረሰብ ክፍሎችም በተገኙበት በሸበል በረንታ ወረዳ የዕድዉሃ ከተማ የእርቅ ማዕድ መርሀ ግብር ተደርጓል።
የደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት ዶክተር ታፈረ መላኩ በዚህ መርሃ ግብር ላይ ባደረጉት ንግግር ይህ በጎ ተግባር ተስፋፍቶ መቀጠል ያለበት መሆኑን አስታውሰው የእርቀ ሰላም ሂደቱ እውን እንዲሆን ቀን ከሌት የሰሩ የሐዲስ ዓለማየሁ የባህል ጥናት ተቋምንና በዘርፉ ውስጥ የሚገኙ ሁሉንም አካላት አመስግነው ከሁሉም በላይ ደግሞ ይህ እርቅ ተፈፃሚ እንዲሆን በግራም በቀኝም በኩል የተገኙ የደም መመለላስ ቀጥተኛ ተሳታፊዎች (ባለ ደሞች) ማለታቸው ነው፤ የዛሬዋ ቀን እንድትመጣ ላደረጉት ቀናነት የተሞላበት ሁለንተናዊ እገዛ አመስግነዋል። ማንኛችንም ላይ የማይገኝ የልብ ንፅህና እናንተ ጋ ይገኛል ያሉት ፕሬዚደንቱ በዚህም ታላቅ ክብርና ምስጋና ይገባችኋል ሲሉም በድጋሚ አመስግነዋል።
የሐዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም ዳይሬክተር ግዛቸው አንዳርጌ (ረ/ፕ) ዩኒቨርሲቲው ከቀረፃቸው ሶስት የልህቀት ማዕከላት መካከል አንደኛው የሀገር በቀል እውቀቶችን ማዳበርና ቋንቋን፣ ባህልንና ስነ-ፅሑፍን ማሳደግ እንደሆነ አስታውሰው የሐዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም መልካም ባህሎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ፤ ጎጅ ልማዶች ደግሞ እንዲወገዱ በማድረግ የማህበረሰቡን ሰላምና ልማት ወደ ተሻለ ደረጃ በማምጣት ለሰላምና እሴት ግንባታ ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል፡፡
በሸበል በረንታ ወረዳ በደም መመላለስ ምክንያት በወንጀሉ ተሳታፊ ያልሆኑ ንፁሃን አካላት የደም መመለሻ እየሆኑ መሬት ፆም አድሯል፤ ህፃናት ካለ አሳዳጊ ቀርተዋል፤ አረጋውያን ያለጧሪ ቀባሪ ቀርተዋል፤ ለትምህርት የደረሱ ልጆች ሳይማሩ ቀርተዋል፤ በርካቶች አካባቢያቸውን ለቀው ተሰደዋል፤ ማህበራዊ ትስስሩ ጠፍቷል፤ ስጋትና ውጥረት ነግሷል። ስለሆነም ይህንን ማህበራዊ ቀውስ ለመቅረፍ ከባህል፣ ከሰላምና ደህንነት፣ ከህግና ከፀጥታ አንፃር ማህበረሰቡን በማሰልጠን፤ የወጣት፣ የሀይማኖት አባት፣ የሀገር ሽማግሌ አደረጃጀት በመፍጠር የማህበረሰቡን አመለካከት በመለወጥ እርቅ አውርደው ሰላማዊ ኑሮ እንዲቀጥሉ መደረጉን ገልፀዋል፡፡
በቀጣይም ይህ ባህላዊ ሽምግልና በህግ በኩል እውቅና አግኝቶ፣ ለደም አድራቂ ሽማግሌዎችም ድጋፍ በመስጠት በመንግስት አደረጃጀት ታቅፈው የእርቅ አባት ሆነው እንዲቀጥሉና በሌሎች ወረዳዎችም ይህ እርቅ ሰላም ተጠናክሮ ቀጥሎ ሀገር አቀፍ እንዲሆን ሌሎች አጋር አካላትም እንዲደግፉ አሳስበዋል፡፡
የምስራቅ ጎጃም ዞን ሰላምና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ አቶ ጌትነት በላይ በርካታ ማህበረሰብ በደም መመላለስ ምክንያት ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እያጋጠማቸው ይገኛል። ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲም ያለውን ችግር ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ በማጥናት ፣ስልጠናዎችን በመስጠትና በመደገፍ በስፋት እየሰራ በመሆኑ አመስግነው በእነሱ በኩልም ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታትና በተደራጀ መልኩ ለመስራት ከሚመለከታቸው አጋር አካላት ጋር በመተባበር እየሰሩ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡
በሸበል በረንታ ወረዳ ደም መመላለስን ለማስቀረት እየሰሩ ከሚገኙ የሀገር ሽማግሌዎች መካከል አቶ አብየ በለው እንደገለፁት ማህበረሰቡ ደም መመላለስን ባለማወቁ እንደ መልካም ባህል በመውሰድ እርስ በርስ ሲጠፋፋ ቆይቷል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ባመጣው መልካም ተግባርም ማህበረሰቡ ደም መመላለስ አስከፊ መሆኑን ተገንዝቦ በመታረቅ ወደ ኑሮውና ማህበራዊ ህይወቱ ተመልሷል ብለዋል፡፡
ባለ ደም የነበሩትና ታርቀው ሰላምን ያገኙት አቶ እያለ ታለማ በበኩላቸው እርቅ መኖሩ ህይወታቸውን እንደቀየረላቸው ይናገራሉ፡፡ ካሁን በፊት በደም መመለስ ምክንያት ሲንገላቱ እንደቆዩና አሁን ላይ ግን ተለውጠው ሰላምና ደህንነት ተቋም ውስጥ በመግባት ሰላምን ለማምጣት እየሰሩ እንደሚገኙ ገልፀው ሁሉም ማህበረሰብ ደም መመላለስ ለማንም እንደማይጠቅም ተገንዝቦ እርቀ ሰላም በማውረድ ወደ መደበኛ ህይወቱ እንዲመለስ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በዚህ መርሀ ግብር ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ፍትህ ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አያሌው አባተ የዕለቱን የእርቅ ማዕድ መርሃ ግብር በመዝጊያ ንግግር እንዲዘጉ የተጋበዙ ሲሆን በንግግራቸውም ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በመምህርነት ሲያገለግሉ በነበሩበት ወቅት ወደ አዲሱ የኃላፊነት ቢሮ ከመግባታቸው በፊት ሸበል በረንታ ወረዳን ጨምሮ በሌሎችም አካባቢዎች ይህ የደም መመላለስ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊትን ለመቀነስ በሚሰሩ ተግባራት ላይ ተሳታፊ እንደነበሩ አስታውሰው ዛሬ ላይ ይህ መልካም ተግባር ፍሬ አፍርቶ እዚህ በመድረሱ የተሰማቸውን ደስታ ገልፀዋል። አያይዘውም አንድን ሰው መግደል ሙሉ ቤተሰብንና ማህበረሰብን መግደል እንደሆነና በአንድ ሰው ብቻ የሚገታ ተግባር አለመሆኑን በመጥቀስ ከእንደዚህ አይነት ተግባር ሁሉም ማህበረሰብ ተቆጥቦ ትኩረቱን ልማትና ሰላማዊ ኑሮ ላይ ማድረግ እንዳለበት አሳስበዋል።
በመጨረሻም የፍትህ ቢሮው በዚህ የደም መመላስ ወይም ሰው መግደል ወንጀል ላይ አዳዲስ የህግ ማዕቀፎችን እያረቀቀ መሆኑን ገልፀው የዕለቱን መርሀ ግብር በይፋ ዘግተዋል።
በዚህ የእርቅ ማዕድ መርሀ ግብር የእርቀ ሰላም ሂደቱ ከመጀመሪያ ጀምሮ እስከፍፃሜው ድረስ እንዲሳካ አስተዋፅኦ ላደረጉ የተለያዩ አካላት የእውቅና ምስክር ወረቀትና የሀገር ባህል ጋቢ የሽልማት ስነ ስርዓትም ተደርጓል።
There are no upcoming events.
DMU Radio Broadcasting . . .