GROW WISER AT THE WATER TOWER
Staff Academic Administrative Graduate
ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ፡- ነሐሴ 11/2014 ዓ.ም (ደ.ማ.ዩ ህዝብ ግንኙነትና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት) የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በሀገራችን ከ16 ዩኒቨርሲቲዎች ለተውጣጡ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጉዳዩ የሚመለከታቸው የግዥ እና ንብረት አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች እንዲሁም የግዥ አፅዳቂ ኮሚቴዎች የተሳተፉበት በዩኒቨርሲቲዎች አከባቢ የሚታዩ የግንባታ ግዥ፣የምክር አገልግሎት ግዥ፣ውል አስተዳደር እና በንብረት አስተዳደርና አወጋገድ ዙሪያ ከነሐሴ 4 እስከ 7 ቀን 2014 ዓ.ም ባሉት ተከታታይ 4 ቀናት በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የሐዲስ ዓለማየሁ የጉባዔ አዳራሽ ከኢፌዲሪ ግዥና ንብረት ባለስልጣን በመጡ አሰልጣኞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ ፡፡
የአቅም ግንባታ ሥልጠናው ዋና ዓላማ ግልፅ፣ ዘመናዊ ቀልጣፋና ውጤታማ የመንግስት ግዥ አፈፃፀምና ንብረት አስተዳደር ማስፈን፣ የመንግስትን ንብረት በጥንቃቄ የመያዝ፣ የመጠቀምና የመቆጣጠር እንዲሁም ንብረቱ አገልግሎቱ ሲያበቃ በወቅቱና በተገቢው መንገድ እንዲወገድ ማስቻል መሆኑ ተገልጿል፡፡
የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ትዉልድን በመቅረፅ ከሚያደርጉት ጎን ለጎን በግዥ አፈፃጸም ተግዳሮቶች፣ በልዩ ግዥ ፍላጎት መበራከት፣ በአቤቱታ እና ጥፋተኝነት ጉዳዮች መብዛት እና በግዥ አፈፃፀም ዙሪያ የሚታዩ የኦዲት ግኝቶች፣ የግንባታ ፕሮጀክቶች የጨረታ ሂደት ዙሪያ የሚታዩ ተግዳሮቶችና የመፍትሄ አቅጣጫዎቻቸዉ እንዲሁም በአጠቃላይ በግዥ ዙሪያ የሚታዩ የግብዓት ጥራት ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው እና ሌሎች የአሰራር ግድፈቶችን በመቅረፍ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ለማስቻል መሆኑን የገለፁት የመንግስት ግዥ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ገበያው ይታይህ ናቸዉ፡፡
መንግስት ከመንገድ ግንባታ ቀጥሎ ከፍተኛ በጀት የሚመድብ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሆኑንና፤ ዩኒቨርሲቲዎች የሚያንቀሳቅሱት በጀትም ከፍተኛ በመሆኑ በየዩኒቨርሲቲዎቹ የሚገኙ የግዥ ባለሙያዎችና የስራ ኃላፊዎች በግዥ ዘርፍ የአስተሳሰብ ለውጥ በማምጣት ገንዘብ ሊያስገኝ የሚችለውን ጥቅም ማስገኘት እንዲችል በትኩረትና በጥንቃቄ መስራት የሚገባቸው መሆኑን ዳይሬክተሩ ስልጠናውን ባስጀመሩበት ወቅት አክለዉ ተናግረዋል፡፡
በስልጠናው ተሳታፊ የነበሩትና በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የግዥና ንብረት አስተዳደር የግዥ ቡድን መሪ አቶ ገመቹ ኃይሉ በዚህ ስልጠና በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚመለከታቸው አካላት ተሳታፊ በመሆናቸው እና ልምዳችንን በመለዋወጣችን የነበሩብንን ብዥታዎች አጥርተናል፤ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ አመራሮችና ባለሙያዎች መኖራቸውም የተሻለ ግንዛቤ እንድናገኝ አድርጎናል ሲሉ ገልፀዋል፡፡
ከወሎ ዩኒቨርሲቲ የመጡት አቶ አቤኔዘር ሀሰን በበኩላቸው የበርካታ ዩኒቨርሲቲዎች አመራሮች እና ባለሙያዎች በመካተታቸው እርስ በርስ እንድንተዋወቅና ልምዳችንን በመለዋወጥ አስቸጋሪ ጉዳዮችን በጋራ እንድፈታ ያስችላል በማለት ገልፀው ለወደፊትም ተጠናክሮ ቢቀጥል ችግሮችን ያቀላል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ግንባታ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ማተቤ አዲስ እንደገለፁት የግንባታ ፕሮጀክት ከፍተኛውን በጀት የሚወስድ በመሆኑ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በግንባታ ግዥና ውል አስተዳደር ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት ስልጠናው ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በግንባታ ስራ ትክክለኛ ዲዛይን፣ሁሉንም ተጫራቾች በእኩል የሚመዝን መስፈርትና የስራ ዝርዝር ካልተዘጋጀ ግንባታው በሚፈለገው መልኩ ሊጠናቀቅ እንደማይችልና እንደሚጓተትም ተናግረዋል ፡፡
በባለስልጣኑ በኩል ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የስራ ኃላፊዎችም ሆነ ለባለሙያዎች በግዥና ንብረት ዙሪያ ተደጋጋሚ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን የሚሰጥ ሲሆን የሚሰጡ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች የባህሪይ ለውጥ በማምጣት በተለይ በዩኒቨርሲቲዎች እየታየ ያለው የኦዲት ክፍተት በአግባቡ መታየትና መሻሻል ይገባዋል ሲሉም ዳይሬክተሩ አቶ ማተቤ አክለዋል፡፡
የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀጅ ኢብሳ በስልጠናዉ ማጠቃሊያ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መለዕክት ሁሉም ሰው በራሱ ሙሉ ስላልሆነ በመወያየትና ልምድ በመለዋወጥ ክፍተቶችን ማጥበብ እንደሚቻል ገልፀው ወደፊት ከስነምግባር ጀምሮ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለማስተካከል የሰው ኃይል በመጨመር በተቻለ መጠን በውይይቱ የተነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስና ችግሮችን ለመቀነስ በስፋት እንደሚሰሩ ቃል ገብተዋል፡፡ ተሳታፊዎች ላሳዩት ተሳትፎና ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲም ለስልጠናው መሳካት ላደረገው አስተዋፅኦ ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበው ተሳታፊዎች ተቋማቸውን፣ሀገራቸውንና ገንዘባቸውን ለመጠበቅ ከዚህ የበለጠ በደንብ መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
በቀጣይ ሁሉም የሀገራችን ዩኒቨርሲቲዎች ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት ብሎም ምርምር ለማካሄድ ግዥ የጀርባ አጥንት በመሆኑ፤ የሚገዙ ግዥዎችን በጊዜና በጥራት መግዛት እንደሚገባ እንዲሁም ህግና ስርዓትን የጠበቀ የግዥና የንብረት አስተዳደር ማስፈን እንደሚጠበቅባቸውም ገልፀዋል፡፡
የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ታፈረ መላኩ (ዶ/ር) የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ባለስልጣን የዩኒቨርሲቲዎችን ችግር ተረድቶ ይህንን ስልጠና በማዘጋጀቱ ምስጋናቸውን አቅርበው ስልጠናው ለስራ መነቃቃትን የሚፈጥርና በግዥ ሂደት የሚፈጠረውን መጉላላት እንደሚቀንስ ገልፀዋል፡፡
በደብረ ማርቆስ ክላስተር የተሰጠውን የአቅም ግንባታ ሥልጠና ከ200 በላይ የግዥና ንብረት ባለሙያዎችና ኃላፊዎች ተሳትፈውበታል፡፡
There are no upcoming events.
DMU Radio Broadcasting . . .