Category Archives: News

  • -

በግንባታ ግዥ፣ በምክር አገልግሎት ግዥ (Consultancy Service) ፣ በውልና በንብረት አስተዳደር እንዲሁም አወጋገድ ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተሰጠ

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ፡- ነሐሴ 11/2014 ዓ.ም (ደ.ማ.ዩ ህዝብ ግንኙነትና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት) የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በሀገራችን ከ16 ዩኒቨርሲቲዎች ለተውጣጡ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጉዳዩ የሚመለከታቸው የግዥ እና ንብረት አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች እንዲሁም የግዥ አፅዳቂ ኮሚቴዎች የተሳተፉበት በዩኒቨርሲቲዎች አከባቢ የሚታዩ የግንባታ ግዥ፣የምክር አገልግሎት ግዥ፣ውል አስተዳደር እና በንብረት አስተዳደርና አወጋገድ ዙሪያ ከነሐሴ 4 እስከ 7 ቀን 2014 ዓ.ም ባሉት ተከታታይ 4 ቀናት በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የሐዲስ ዓለማየሁ የጉባዔ አዳራሽ ከኢፌዲሪ ግዥና ንብረት ባለስልጣን በመጡ አሰልጣኞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ ፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is photo1.jpg

የአቅም ግንባታ ሥልጠናው ዋና ዓላማ ግልፅ፣ ዘመናዊ ቀልጣፋና ውጤታማ የመንግስት ግዥ አፈፃፀምና ንብረት አስተዳደር ማስፈን፣ የመንግስትን ንብረት በጥንቃቄ የመያዝ፣ የመጠቀምና የመቆጣጠር እንዲሁም ንብረቱ አገልግሎቱ ሲያበቃ በወቅቱና በተገቢው መንገድ እንዲወገድ ማስቻል መሆኑ ተገልጿል፡፡

የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ትዉልድን በመቅረፅ ከሚያደርጉት ጎን ለጎን በግዥ አፈፃጸም ተግዳሮቶች፣ በልዩ ግዥ ፍላጎት መበራከት፣ በአቤቱታ እና ጥፋተኝነት ጉዳዮች መብዛት እና በግዥ አፈፃፀም ዙሪያ የሚታዩ የኦዲት ግኝቶች፣ የግንባታ ፕሮጀክቶች የጨረታ ሂደት ዙሪያ የሚታዩ ተግዳሮቶችና የመፍትሄ አቅጣጫዎቻቸዉ እንዲሁም በአጠቃላይ በግዥ ዙሪያ የሚታዩ የግብዓት ጥራት ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው እና ሌሎች የአሰራር ግድፈቶችን በመቅረፍ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ለማስቻል መሆኑን የገለፁት የመንግስት ግዥ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ገበያው ይታይህ ናቸዉ፡፡

መንግስት ከመንገድ ግንባታ ቀጥሎ ከፍተኛ በጀት የሚመድብ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሆኑንና፤ ዩኒቨርሲቲዎች የሚያንቀሳቅሱት በጀትም ከፍተኛ በመሆኑ በየዩኒቨርሲቲዎቹ የሚገኙ የግዥ ባለሙያዎችና የስራ ኃላፊዎች በግዥ ዘርፍ የአስተሳሰብ ለውጥ በማምጣት ገንዘብ ሊያስገኝ የሚችለውን ጥቅም ማስገኘት እንዲችል በትኩረትና በጥንቃቄ መስራት የሚገባቸው መሆኑን ዳይሬክተሩ ስልጠናውን ባስጀመሩበት ወቅት አክለዉ ተናግረዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is photo2.jpg

በስልጠናው ተሳታፊ የነበሩትና በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የግዥና ንብረት አስተዳደር የግዥ ቡድን መሪ አቶ ገመቹ ኃይሉ በዚህ ስልጠና በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚመለከታቸው አካላት ተሳታፊ በመሆናቸው እና ልምዳችንን በመለዋወጣችን የነበሩብንን ብዥታዎች አጥርተናል፤ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ አመራሮችና ባለሙያዎች መኖራቸውም የተሻለ ግንዛቤ እንድናገኝ አድርጎናል ሲሉ ገልፀዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is photo3.jpg

ከወሎ ዩኒቨርሲቲ የመጡት አቶ አቤኔዘር ሀሰን በበኩላቸው የበርካታ ዩኒቨርሲቲዎች አመራሮች እና ባለሙያዎች በመካተታቸው እርስ በርስ እንድንተዋወቅና ልምዳችንን በመለዋወጥ አስቸጋሪ ጉዳዮችን በጋራ እንድፈታ ያስችላል በማለት ገልፀው ለወደፊትም ተጠናክሮ ቢቀጥል ችግሮችን ያቀላል ብለዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is photo4.jpg

የኢትዮጵያ ግንባታ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ማተቤ አዲስ እንደገለፁት የግንባታ ፕሮጀክት ከፍተኛውን በጀት የሚወስድ በመሆኑ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት  በግንባታ ግዥና ውል አስተዳደር ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት ስልጠናው ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በግንባታ ስራ ትክክለኛ ዲዛይን፣ሁሉንም ተጫራቾች በእኩል የሚመዝን መስፈርትና የስራ ዝርዝር ካልተዘጋጀ ግንባታው በሚፈለገው መልኩ ሊጠናቀቅ እንደማይችልና እንደሚጓተትም ተናግረዋል ፡፡

በባለስልጣኑ በኩል ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የስራ ኃላፊዎችም ሆነ ለባለሙያዎች  በግዥና ንብረት ዙሪያ ተደጋጋሚ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን የሚሰጥ ሲሆን የሚሰጡ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች የባህሪይ ለውጥ በማምጣት በተለይ በዩኒቨርሲቲዎች እየታየ ያለው የኦዲት ክፍተት በአግባቡ መታየትና መሻሻል ይገባዋል ሲሉም ዳይሬክተሩ አቶ ማተቤ አክለዋል፡፡

የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀጅ ኢብሳ በስልጠናዉ ማጠቃሊያ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መለዕክት ሁሉም ሰው በራሱ ሙሉ ስላልሆነ በመወያየትና ልምድ በመለዋወጥ ክፍተቶችን ማጥበብ እንደሚቻል ገልፀው ወደፊት ከስነምግባር ጀምሮ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለማስተካከል የሰው ኃይል በመጨመር በተቻለ መጠን በውይይቱ የተነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስና ችግሮችን ለመቀነስ በስፋት እንደሚሰሩ ቃል ገብተዋል፡፡ ተሳታፊዎች ላሳዩት ተሳትፎና ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲም ለስልጠናው መሳካት ላደረገው አስተዋፅኦ ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበው ተሳታፊዎች ተቋማቸውን፣ሀገራቸውንና ገንዘባቸውን ለመጠበቅ ከዚህ የበለጠ በደንብ መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

በቀጣይ ሁሉም የሀገራችን ዩኒቨርሲቲዎች ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት ብሎም ምርምር ለማካሄድ ግዥ የጀርባ አጥንት በመሆኑ፤ የሚገዙ ግዥዎችን በጊዜና በጥራት መግዛት እንደሚገባ እንዲሁም ህግና ስርዓትን የጠበቀ የግዥና የንብረት አስተዳደር ማስፈን እንደሚጠበቅባቸውም ገልፀዋል፡፡

የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ታፈረ መላኩ (ዶ/ር) የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ባለስልጣን የዩኒቨርሲቲዎችን ችግር ተረድቶ ይህንን ስልጠና በማዘጋጀቱ ምስጋናቸውን አቅርበው ስልጠናው ለስራ መነቃቃትን የሚፈጥርና በግዥ ሂደት የሚፈጠረውን መጉላላት እንደሚቀንስ ገልፀዋል፡፡

በደብረ ማርቆስ ክላስተር የተሰጠውን የአቅም ግንባታ ሥልጠና ከ200 በላይ የግዥና ንብረት ባለሙያዎችና ኃላፊዎች ተሳትፈውበታል፡፡


  • -

University initiates community-based projects

 

DEBRE MARKOS- University of Debre Markos said that it has initiated projects aiming at supporting local community through in agricultural, environmental and cultural researches.

In Exclusive interview with Ethiopian Press Agency (EPA), Debre Markos University President, Tafere Melaku (PhD) said that projects targeting at supporting the local community, which is known for its productive agricultural activities, are being implemented, and about 32 projects which have been designed by the University are under implementation.

“The categorization of Universities based on their excellence puts Debre Markos University as applied University. So, we are conducting applied researches that could help launch community based projects.”

“We have assessed that previous projects were insignificant compared to the existing ones. This year, we have exerted efforts on developmental projects.”

Now, the University is implementing agricultural projects including summer season wheat irrigation and fruit breading projects in Debre Elias, Gozamin, and Bure as well as in some other areas of East Gojjam Zone, he added.

The University has also run a project aiming at afforesting the Abay [Nile] valley with bamboo trees.

“The Abay gorge can be one of national economic sources; hence we are cooperating with Selale University.

Besides, the gorge is very comparable area to the Chinese bamboo forest areas by its ecology. Chinese are familiar with bamboo furniture production; so we can do the same thing if we succeed with this project,” he stated.

The University has also been working to afforest the Choke Mountain and treat acidic soil in Baso Liben Woreda.

Irrigation, Fishery, bee keeping, cultural and indigenous knowledge development projects have been initiated by the University so far, it was learnt.

 


  • -

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የደም መመላለስ ጎጂ ልማዳዊ ባህልን ለማስቆም ባደረገው ጥረት በሸበል በረንታ ወረዳ ተግባራዊ ለውጥ ማምጣቱ ተገለፀ

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ሐምሌ 19/2014 ዓ.ም (ደ.ማ.ዩ ህዝብ ግንኙነትና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት) ደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ በምስራቅ ጎጃም ዞን በተለይም ደግሞ በሸበል በረንታ ወረዳ እየተፈፀመ የሚገኘውን ጎጅ ልማዳዊ የደም መመላለስ ባህል ለማስቀረትና ማህበረሰቡ ሰላማዊ ህይወት እንዲኖረው ለማስቻል በዩኒቨርሲቲው ሐዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም በኩል የሁለት ዓመታት ፕሮጀክት በመቅረፅ በስፋት እየሰራ ይገኛል፡፡

በዚህም በ2013 እና በ2014 ዓ.ም የማህበረሰቡን አመለካከት በመለወጥ 59 እርቆች የተፈፅመው እና ቀያቸውን እርቀው የተበተኑ የገዳይና ሟች ቤተሰቦችም ወደ ቀያቸዉ ተመልሰዉ መደበኛ ኑሯቸውን እየመሩና ወደ ልማት እየተመለሱ እንደሚገኙ በአካል ተገኝተን ለማረጋገጥ ችለናል፡፡

ይህን የእርቀ ሰላም ሂደት በማስመልከት የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት ዶ/ር ታፈረ መላኩ፣ ም/ፕሬዚደንቶች፣ ዳይሬክተሮች፣ዲኖችና የልዩ ልዩ ስራ ክፍል ኃላፊዎችና ባለሙያዎች እንዲሁም የአማራ ክልል ፍትህ ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አያሌው አባተን ጨምሮ የምስራቅ ጎጃም ዞን ም/አስተዳዳሪ፣ የሸበል በረንታ ዋና አስተዳዳሪ እና የፀጥታ አካላት እንዲሁም የዚህ እርቅ ስነ ስርዓት ቀጥተኛ ባለጉዳዮች(ባለ-ደሞች) እና አስታራቂ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች እና ልዩ ልዩ የማህበረሰብ ክፍሎችም በተገኙበት በሸበል በረንታ ወረዳ የዕድዉሃ ከተማ የእርቅ ማዕድ መርሀ ግብር ተደርጓል።

This image has an empty alt attribute; its file name is erik1.jpg

የደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት ዶክተር ታፈረ መላኩ በዚህ መርሃ ግብር ላይ ባደረጉት ንግግር ይህ በጎ ተግባር ተስፋፍቶ መቀጠል ያለበት መሆኑን አስታውሰው የእርቀ ሰላም ሂደቱ እውን እንዲሆን ቀን ከሌት የሰሩ የሐዲስ ዓለማየሁ የባህል ጥናት ተቋምንና በዘርፉ ውስጥ የሚገኙ ሁሉንም አካላት አመስግነው ከሁሉም በላይ ደግሞ ይህ እርቅ ተፈፃሚ እንዲሆን በግራም በቀኝም በኩል የተገኙ የደም መመለላስ ቀጥተኛ ተሳታፊዎች (ባለ ደሞች) ማለታቸው ነው፤ የዛሬዋ ቀን እንድትመጣ ላደረጉት ቀናነት የተሞላበት ሁለንተናዊ እገዛ አመስግነዋል። ማንኛችንም ላይ የማይገኝ የልብ ንፅህና እናንተ ጋ ይገኛል ያሉት ፕሬዚደንቱ በዚህም ታላቅ ክብርና ምስጋና ይገባችኋል ሲሉም በድጋሚ አመስግነዋል።

This image has an empty alt attribute; its file name is erik2.jpg

የሐዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም ዳይሬክተር ግዛቸው አንዳርጌ (ረ/ፕ) ዩኒቨርሲቲው ከቀረፃቸው ሶስት የልህቀት ማዕከላት መካከል አንደኛው የሀገር በቀል እውቀቶችን ማዳበርና ቋንቋን፣ ባህልንና ስነ-ፅሑፍን ማሳደግ እንደሆነ አስታውሰው የሐዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም መልካም ባህሎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ፤ ጎጅ ልማዶች ደግሞ እንዲወገዱ በማድረግ የማህበረሰቡን ሰላምና ልማት ወደ ተሻለ ደረጃ በማምጣት ለሰላምና እሴት ግንባታ ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል፡፡

በሸበል በረንታ ወረዳ በደም መመላለስ ምክንያት በወንጀሉ ተሳታፊ ያልሆኑ ንፁሃን አካላት የደም መመለሻ እየሆኑ መሬት ፆም አድሯል፤ ህፃናት ካለ አሳዳጊ ቀርተዋል፤ አረጋውያን ያለጧሪ ቀባሪ ቀርተዋል፤ ለትምህርት የደረሱ ልጆች ሳይማሩ ቀርተዋል፤ በርካቶች አካባቢያቸውን ለቀው ተሰደዋል፤ ማህበራዊ ትስስሩ ጠፍቷል፤ ስጋትና ውጥረት ነግሷል። ስለሆነም ይህንን ማህበራዊ ቀውስ ለመቅረፍ ከባህል፣ ከሰላምና ደህንነት፣ ከህግና ከፀጥታ አንፃር ማህበረሰቡን በማሰልጠን፤ የወጣት፣ የሀይማኖት አባት፣ የሀገር ሽማግሌ አደረጃጀት በመፍጠር የማህበረሰቡን አመለካከት በመለወጥ እርቅ አውርደው ሰላማዊ ኑሮ እንዲቀጥሉ መደረጉን ገልፀዋል፡፡

በቀጣይም ይህ ባህላዊ ሽምግልና በህግ በኩል እውቅና አግኝቶ፣ ለደም አድራቂ ሽማግሌዎችም ድጋፍ በመስጠት በመንግስት አደረጃጀት ታቅፈው የእርቅ አባት ሆነው እንዲቀጥሉና በሌሎች ወረዳዎችም ይህ እርቅ ሰላም ተጠናክሮ ቀጥሎ ሀገር አቀፍ እንዲሆን ሌሎች አጋር አካላትም እንዲደግፉ አሳስበዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is erik3.jpg

የምስራቅ ጎጃም ዞን ሰላምና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ አቶ ጌትነት በላይ በርካታ ማህበረሰብ በደም መመላለስ ምክንያት ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እያጋጠማቸው ይገኛል። ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲም ያለውን ችግር ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ በማጥናት ፣ስልጠናዎችን በመስጠትና በመደገፍ በስፋት እየሰራ በመሆኑ አመስግነው በእነሱ በኩልም ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታትና በተደራጀ መልኩ ለመስራት ከሚመለከታቸው አጋር አካላት ጋር በመተባበር እየሰሩ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is erik4.jpg

በሸበል በረንታ ወረዳ ደም መመላለስን ለማስቀረት እየሰሩ ከሚገኙ የሀገር ሽማግሌዎች መካከል አቶ አብየ በለው እንደገለፁት ማህበረሰቡ ደም መመላለስን ባለማወቁ እንደ መልካም ባህል በመውሰድ  እርስ በርስ ሲጠፋፋ ቆይቷል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ባመጣው መልካም ተግባርም ማህበረሰቡ ደም መመላለስ አስከፊ መሆኑን ተገንዝቦ በመታረቅ ወደ ኑሮውና ማህበራዊ ህይወቱ ተመልሷል ብለዋል፡፡

ባለ ደም የነበሩትና ታርቀው ሰላምን ያገኙት አቶ እያለ ታለማ በበኩላቸው እርቅ መኖሩ ህይወታቸውን እንደቀየረላቸው ይናገራሉ፡፡ ካሁን በፊት በደም መመለስ ምክንያት ሲንገላቱ እንደቆዩና አሁን ላይ ግን ተለውጠው ሰላምና ደህንነት ተቋም ውስጥ በመግባት ሰላምን ለማምጣት እየሰሩ እንደሚገኙ ገልፀው ሁሉም ማህበረሰብ ደም መመላለስ ለማንም እንደማይጠቅም ተገንዝቦ እርቀ ሰላም በማውረድ ወደ መደበኛ ህይወቱ እንዲመለስ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is erik5.jpg

በዚህ መርሀ ግብር ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ፍትህ ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አያሌው አባተ የዕለቱን የእርቅ ማዕድ መርሃ ግብር በመዝጊያ ንግግር እንዲዘጉ የተጋበዙ ሲሆን በንግግራቸውም ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በመምህርነት ሲያገለግሉ በነበሩበት ወቅት ወደ አዲሱ የኃላፊነት ቢሮ ከመግባታቸው በፊት ሸበል በረንታ ወረዳን ጨምሮ በሌሎችም አካባቢዎች ይህ የደም መመላለስ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊትን ለመቀነስ በሚሰሩ ተግባራት ላይ ተሳታፊ እንደነበሩ አስታውሰው ዛሬ ላይ ይህ መልካም ተግባር ፍሬ አፍርቶ እዚህ በመድረሱ የተሰማቸውን ደስታ ገልፀዋል። አያይዘውም አንድን ሰው መግደል ሙሉ ቤተሰብንና ማህበረሰብን መግደል እንደሆነና በአንድ ሰው ብቻ የሚገታ ተግባር አለመሆኑን በመጥቀስ ከእንደዚህ አይነት ተግባር ሁሉም ማህበረሰብ ተቆጥቦ ትኩረቱን ልማትና ሰላማዊ ኑሮ ላይ ማድረግ እንዳለበት አሳስበዋል።

በመጨረሻም የፍትህ ቢሮው በዚህ የደም መመላስ ወይም ሰው መግደል ወንጀል ላይ አዳዲስ የህግ ማዕቀፎችን እያረቀቀ መሆኑን ገልፀው የዕለቱን መርሀ ግብር በይፋ ዘግተዋል።

በዚህ የእርቅ ማዕድ መርሀ ግብር የእርቀ ሰላም ሂደቱ ከመጀመሪያ ጀምሮ እስከፍፃሜው ድረስ እንዲሳካ አስተዋፅኦ ላደረጉ የተለያዩ አካላት የእውቅና ምስክር ወረቀትና የሀገር ባህል ጋቢ የሽልማት ስነ ስርዓትም ተደርጓል።


  • -

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች አስመረቀ

 

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ሀምሌ 16/2014 ዓ.ም (ደ/ማ/ዩ፡- ህዝብ ግንኙነትና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት) ደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ በመደበኛው፣በማታው እና በተከታታይ የትምህርት መርሀ ግብሮች በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን 2212 ተማሪዎች የፌደራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ፣ተጋባዥ እንግዶች እንዲሁም የሚዲያ ባለሙያዎች በተገኙበት ለ14 ኛ ጊዜ ሀምሌ 16/2014 ዓ.ም በድምቀት አስመርቋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is 26-1.jpg

በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ታፈረ መላኩ (ዶ/ር) ተመራቂዎች አለም አቀፉን የኮሮና ወረርሽኝ እና በሀገሪቱ የነበረውን ጦርነት ተቋቁማችሁ ለዚህ ስኬት በመብቃታችሁ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስተር የአፕላይድ ዩኒቨርሲቲ ሆኖ መመደቡን ተከትሎ በግብርና፣ በሀገር በቀል ዕውቀትና በጤና ዘርፎች በትኩረት እየሰራ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡

በ1999 ዓ.ም ስራውን የጀመረው ዩኒቨርሲቲው እስካሁን 54 ሺህ 874 ተማሪዎችን ማስመረቁን ገልፀው በአሁኑ ሰዓት 63 የመጀመሪያ ዲግሪ ፣ 65 ሁለተኛ ዲግሪ እንዲሁም 9 ሶስተኛ ዲግሪ ፕሮግራሞች እንዳሉት ተናግረዋል፡፡

This image has an empty alt attribute; its file name is 26-2.jpg

የምረቃ ስነ-ስርዓቱ የክብር እንግዳ ፕሮፌሰር በላይ ካሳ ሲሆኑ ለተመራቂ ተማሪዎች የስራ መመሪያ መልዕክት አስተላልፈዋል።

This image has an empty alt attribute; its file name is 26-3.jpg

በአሁኑ ስዓት የአማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት (አመልድ) ዋና ዳይሬክተር ሆነው በማገልገል ላይ የሚገኙት ዶ/ር ዓለማየሁ ዋሴ  ለተመራቂ ተማሪዎች ተጨማሪ የህይወት ክህሎት ንግግር አድርገዋል።

This image has an empty alt attribute; its file name is 26-4.jpg

በዕለቱ ከኮሌጆች፣ተቋማት እና ት/ቤቶች ከ1ኛ እስከ ሶስተኛ ደረጃ ለያዙ ተመራቂዎች የምስክር ወረቀት፣ አንደኛ ደረጃ ለያዙ ተማሪዎች የሜዳሊያ እንዲሁም ከአጠቃላይ ከወንዶችና ሴቶች 1ኛ ደረጃ ለያዙ ተመራቂዎች የዋንጫ ሽልማት ተበርክቷል፡፡ከአጠቃላይ ወንድ ተማሪዎች 3.96 በማምጣት 1ኛ ደረጃ የያዘው ከተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ ደሳለኝ ቢራራ ሲሆን ከአጠቃላይ ሴት ተመራቂዎች 3.93 በማምጣት 1ኛ የሆነችው ደግሞ ከህክምና ትምህርት ቤት እጅጋየሁ ይግዛው ናት፡፡

እነዚህ የዋንጫ ተሸላሚዎች ለዚህ ክብር በመብቃታቸው መደሰታቸውን በመግለፅ የነበረውን ወቅታዊ ችግር ተቋቁመው ለዚህ ዕድል መብቃታቸው ደግሞ ስኬታቸውን ልዩ እንደሚያደርገው ገልፀዋል፡፡

በዋናው ግቢ የተከናወነው የተማሪዎች ምረቃ ስነ-ስርዓት በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የቀጥታ ስርጭት ሽፋን ያገኘ ሲሆን በአሚኮ ዩቱዩብ ቻናል ላይም እንደሚገኝ እየጠቆምን ሙሉ ዝግጅቱን ለመመልከት ለምትፈልጉ ከታች ሊንኩን አስቀምጠናል።

https://youtu.be/GeUYE89Sf7k


Search DMU

Upcoming Events

There are no upcoming events.

Partners

DMU Radio Broadcasting . . .